19 September 2018

አምባገነንነትን በጀብደኝነት ከተካን ወደ አምባገነንነት መመለሳችን አይቀርም


ጥቂት 'የፖለቲካ አክቲቪስቶች' በኢትዮጵያ የተከሰተውን ለውጥ በግላቸው ያመጡት እንደሆነ ደጋግመው ሲያወሩ ይሰማል:: ግልፅ መሆን ያለበት የተገኘው ውጤት የመላው ኢትዮጵያውያን የዘመናት የትግል ውጤት መሆኑን ነው:: ግለሰቦች ተነስተው ለውጡን እኔ ነኝ ያመጣሁት፤ እንደፈለገኝ መሆን እችላለሁ ሲሉ ዝም ብለን ልናያቸው አይገባም:: ዝምታ ባበዛን ቁጥር እነዚህ ግለሰቦች በጀብደኝነት ናላቸው ይዞራል:: በጀብደኝነት የሚሰራ ስራ ደግሞ ሚዛናዊነትን ሊያጣ ይችላል:: ችኩልነትም ይኖረዋል:: ለዚህም ነው ከአሁኑ ጥንቃቄ ማድረግ የሚገባን:: ሳይቃጠል በቅጠል ይባላል::

ከመንግሥት ከተፎካካሪ ፓርቲዎችና ከሚዲያው ምን ይጠበቃል?

1. ለሰላምና እርቅ በጋራ መሥራት - በሀገራችን ለዘመናት ሲዘራ የኖረው ዘርን መሰረት ያደረገ ቅስቀሳ በህዝቦች መካከል አለመተማመን መፍጠሩ አልቀረም:: ይህ አለመተማመን በለውጡ ላይ ተፅዕኖ አለው:: ተፅዕኖውም በግልፅ እየታየ ነው:: በህዝቦች መካከል ግልፅ የሆነ ውይይት ማድረግ አስፈላጊ ነው:: ችግሩ ምንድን ነው? የመፍትኄ ሃሳቡስ ብሎ መጠየቅና ጥልቅ የሆነ ውይይት ማድረግ ይገባል:: ችግሮችን አድበስብሰን ማለፍ የለብንም:: ችግሮቻችንን በውይይት የመፍታት ባህል ማዳበረ አለብን:: በሃሳብ አለመግባባት ወይም አለመስማማት ወደ ፀብ ሊወስደን አይገባም:: ላለመስማማት ተስማምተን አብረን መጓዝ እንችላለን (We need to agree to disagree):: ይህ ትልቅ የአመራር ብቃት ይጠይቃል::

2. ለተቋማት ግንባታ ቅድሚያ መስጠት - የተጀመረው ለውጥ መቀጠል የሚችለውና ዘላቂ የሚሆነው ለዲሞክራሲ ግንባታ አስፈላጊ የሆኑ ተቋማት በጊዜው ሲገነቡ ነው:: ከግለሰብም ሆነ ከፖለቲካ ፓርቲ ተፅዕኖ ነፃ የሆኑ ተቋማት ከገነባን ብቻ ነው በኢትዮጵያችን ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ማስፈን የምንችለው:: እነዚህ ተቋማት ዋስትናዎቻችን ናቸው:: ስለዚህም ቅድሚያ ልንሰጣቸው ይገባል::

3. የሚዲያ ነፃነትና ተጠያቂነት - በሀገራችን ያሉት የሚዲያ ተቋማት ነፃነት ሊኖራቸው የሚገባውን ያህል ተጠያቂነት እንዳለባቸውም መዘንጋት የለባቸውም:: ጀብደኝነትንና የጥላቻ ወሬዎችን በተደጋጋሚ ማስተናገድ ዋጋ ያስከፍላል:: ለሀገርና የህዝብ ደህንነት ስጋት የሆኑ መልዕክቶች ከመተላለፋቸው በፊት ጥንቃቄ ማድረግ አስፈላጊ ነው:: የተጠያቂነት ባህልን ማዳበር ይገባል::

4. የሥራ ፈጠራና የኢኮኖሚ ግንባታ - በሀገራችን የሥራ አጥነት በስፋት መኖሩን መዘንጋት የለብንም:: ብዙ ሥራ መስራት የሚችሉ ነገር ግን የሥራ እድሉን ያላገኙ ወጣቶች እንዳሉ የታወቀ ሲሆን ይህንን እምቅ ኃይል ለሀገር ግንባታ ለመጠቀም ሁኔታዎችን ማመቻቸት አለብን:: ከሀገራችን ሀብቶች አንዱ የሰው ኃይላችን ነው:: የሥራ ፈጣሪነትን በማበረታታት ይህን እምቅ ኃይል ለሀገር ግንባታ ልናውለው ይገባል:: ይህ ኃይል የሀገራችን ኢኮኖሚያዊ ዋልታና ደጀን መሆን ይችላል:: ኢንቬስትመንት ወደ ሀገራችን እንዲገባና ህዝባችንም ተጠቃሚ እንዲሆን መንግስትም ሆነ የሚመለከታቸው አካላት በሙሉ ሳያሰልሱ መስራት አለባቸው:: በተጓዳኝም ሲቪል ሰርቪሱ ከተንዛዛ አሰራርና ሙሰኝነት ነፃ መሆን አለበት:: ለዚህም መሳካት ሁሉም የበኩሉን ማድረግ ይጠበቅበታል::

ሀገራችንን የማገዝና የማሳደግ ግዴታው የሁለችንም ነው:: ዛሬ ነገ ሳንል ሀገር ግንባታ ላይ ማተኮር አለብን::

The Global Refugee Forum – time for meaningful participation of Refugees

  As the Global Refugee Forum takes place between 13 - 15 December 2023 in Switzerland, it is vital that we have meaningful participation of...