2 August 2021

ኢትዮጵያውያን ማንንም አንጠላም - ነገር ግን ሃገራችንን ሲነኩብን ዝም አንልም

 

እ.አ.አ ኖቬምበር 2020 መጀመሪያ ላይ ህውሃት በኢትዮጵያ የመከላከያ ጦር ላይ ያደረገውን ጥቃት ተከትሎ በትግራይ የተቀሰቀሰው ጦርነት ብዙ ዋጋ አስከፍሏል። በዚህ ጦርነት የብዙሃን ህይወት የጠፋ ከመሆኑም በላይ፤ በዙሃን ወገኖቻችን የአካል መጉድል፣ መፈናቀልና ልዩ ልዩ ጉዳት የደረሰባቸው መሆኑ ይታወቃል። የጦርነት ምንም ደግ የለውም።

ይህን ጦርነት አሳዛኝ የሚያደርገው  በወንድማማቾችና እህትማማቾች መካከል የሚደረግ የተወሰኑ የስልጣን ጥመኞችን በዕብሪት የተሞላ ፍላጎት ለማሟላት በሚንቀሳቀስ አሸባሪ ኃይልና በተቃራኒው ደግሞ የኢትዮጵያን ህዝብና ሀገሪቷን የመጠበቅ ኃላፊነት ባለበትና በብዙሃኑ የኢትዮጵያ ህዝብ ድጋፍ ባለው የኢትዮጵያ ጦር ሰራዊት መካከል የሚደረግ ጦርነት መሆኑ ነው።

እንደሚታወቀው ህውሃት በኢትዮጵያ ለ27 ዓመታት በስልጣን በቆየበት ዘመን እጅግ በጣም አምባገነን ከመሆኑ የተነሳ እጅግ በጣም ብዙ ዘግናኝ የሆኑ ተግባራትን ሲፈፅም የቆየ ነው። ህወሃት በስልጣን ለመቆየት የኢትዮጵያን ህዝብ በዘር መከፋፈል ብቸኛው አማራጭ አድርጎ ስላመነ ህዝባችንን ለመከፋፈል የተቻለውን ሁሉ ሲያደርግ ቆይቷል። በብሄሮች መካከል ጥርጣሬ እንዲኖር፤ የጋራ አጀንዳ እንዳይኖርና ኢትዮጵያዊነት እንዲከስም ህወሃት ብዙ ሰርቷል።

ህወሃት ኖቬምበር 2020 ላይ የመከላከያ ኃይላችን ላይ ጥቃት ሲያደርግ የተለያዩ እሳቤዎችን ከገንዛቤ በመክተት እንደሆነ ይገመታል። በህወሃት ዕምነት የኢትዮጵያ ህዝብ ተከፋፍሏል። በህወሃት ዕምነት የኢትዮጵያን ሰራዊት በቀላሉ በማሸነፍ ስልጣን በቀላሉ መያዝ ይቻላል የሚል የተሳሳተና በዕብሪት የተሞላ ግንዛቤ ነበር። በህዋሃት ዕምነት በኢትዮጵያ የመንግስት ስልጣን መያዝ ብቻ ሳይሆን በኤርትራም የመንግስት ለውጥ ማምጣት ይቻላል የሚል እጅግ በጣም ሌሎችን አሳንሶ የማየት፤ እራስን ያለማወቅና የማግዘፍ ዝንባሌ ነበር።

በህዋሃትና ጥቂት ደጋፊዎቹ ውስጥ የተፈጠረው የበላይነት ስሜት የሌሎችን ጥንካሬ ለማየት እንዲሳናቸው አድርጓቸዋል። ለዚህም ሕወሃት ጦርነቱ እንደተጀመረ ይስጥ የነበረው መግለጫ ትልቅ ግንዛቤ ይሰጣል።

 

የህወሃቱ ሴኩቱሬ ጌታቸው ስለ ህወሃት አጥቂነትና ጠንካራነት ሲነግረን ህወሃት መብረቃዊ ጥቃት ማድረግ ብቸኛው አማራጭ እንደነበረ ነግሮናል። ይህ ትዕቢት የተሞላበት ንግግር ብዙዎችን አስቆጥቷል። ህወሃት በወቅቱ ጥቃት ሲፈፅም የነበረው ግንዛቤ መከላከያን ጨምሮ የተቀረው ህዝብ ምላሽ የማይሰጥና እራሱን መከላከል የማይችል አድርጎ አሳንሶ የማየት ዝንባሌ ነው። በሃገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያለው የህወሃት ኃይልና ደጋፊ ትልቅ የሆነ የግንዛቤ ችግር ያለበት ባይሆን ይህ ጦርነት እዚህ ደረጃ አይደርስም ነበር። እነ አሉላ ሰለሞን ጦርነት ባህላዊ ጨዋታችን ነው ሲሉን፤ እነ ስየ አብርሃ ደግሞ ስለ ጦርነት እኛ ፊት እንዳታወሩ ይሉን ነበር። ይባስ ብሎ ፈረንጆቹ እነ ኸርማን ኮህንና ሌሎች አውሮፓውያን ህወሃትን ከሌላ ዓለም የመጣ ለማስመሰል ሞክረዋል።

ህወሃት ራሱን በራሱ ጠልፎ ከወደቀ በኋላ እንዴት ብቻዬን እውድቃለሁ በሚል ጦርነቱን ወደ ሌሎች ክልሎችና ሉዓላዊት ሀገር ወደ ሆነችው ኤርትራ ለመውሰድ ብዙ ጥሯል። ህወሃት አልተሳካለትም እንጂ የአፍሪካ ቀንድና ቀጠናውን ጦርነት ውስጥ ለመክተት ያላደረገው ጥረት የለም።

ህወሃት የኢትዮጵያን ህዝብ በዳይ ሆኖ ሳለ የምዕራብ ዓለም ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ በኤክስፐርትነትና በስብዓዊ መብት ተቆርቋሪነት ስም ድብቅ ዓላማቸውን ከሚያከናውኑ ግለሰቦችና ተቋማት ከፍተኛ ድጋፍ ሲያገኝ ቆይቷል።

ምዕራባውያን ፖለቲከኞችና ሚዲያዎች ለህወሃት ድጋፍ ከመስጠት በተጨማሪ በኢትዮጵያ ላይ አላስፈላጊና መርህ አልባ የሆነ ተፅዕኖ ሲያደርጉ የቆዩ ሲሆን አንዳንዶቹ የአሜሪካና የአውሮፓ ባለስልጣናትና ቢሮክራት በኢትዮጵያ የመንግስት ለውጥ እንዲኖር እየሰሩ መሆናቸውን የሚያሳዩ ምልክቶች እየታዩ ነው። በዩጎዝላቪያ፣ ኢራቅ፣ ሊቢያ፣ ሶሪያና የመን እንዳደረጉት ሁሉ በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ውስጥ ጣልቃ ለመግባት እየተዘጋጁ መሆናቸውን የሚያሳዩ ምልክቶች እየታዩ ነው።

የምዕራቡ ዓለም ፖለቲከኞች ጋ የግንዛቤ ችግር ያለ ይመስላል። ኢትዮጵያ የራሷ የሆኑ የቆዩና በመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ውስጥ ዘልቀው የገቡ የጋራ እሴቶች መኖራቸውን፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ለጠላት መቸም ቢሆን ተንበርክኮ የማያውቅ መሆኑን፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ከመቸውም በላይ በአንድነት ሆኖ ለሃገሩ ዘብ ለመቆም ዝግጁ መሆኑን፤ የኢትዮጵያ ጉዳይ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የመላው አፍሪካና የጥቁር ህዝቦች ጉዳይም ጭምር መሆኑን ግንዛቤ ውስጥ ያለማስገባት ሁኔታ ይታያል።

ኢትዮጵያውያን በፖለቲካ አመለካከት ልንለያይ እንችል ይሆናል። በተለያዪ ዓለማት ተበትነን እየኖርንም ሊሆን ይችላል። በሃገራችን ጉዳይ ግን በፍፁም አንደራድርም

ኢትዮጵያ ለሌሎች ሃገራት የምትሰጠውን ክብር ራሷም ማግኘት አለባት። ስለዚህ የአሜሪካና የአውሮፓ ፖለቲከኞችና ቢሮክራት በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ላይ የሚያደርጉትን ጣልቃገብነት መታገል ግዴታችን ነው ። ከማንም በፊት የኢትዮጵያን ጥቅም ማስጠበቅ የምንችለው እኛው ራሳችን ኢትዮጵያውያን ነን:: ኢትዮጵያውያን በፍፁም ችላ እንዳንል። 

ኢትዮጵያውያን ማንንም አንጠላም። ነገር ግን ሃገራችንን ሲነኩብን ዝም አንልም። በኢትዮጵያ ጉዳይ ዝምታ የለም። በፍፁም።

 

The Global Refugee Forum – time for meaningful participation of Refugees

  As the Global Refugee Forum takes place between 13 - 15 December 2023 in Switzerland, it is vital that we have meaningful participation of...