29 August 2018

ዲያስፖራው ለሀገሩ


በውጭ የምንኖር ኢትዮጵያውያን በአብዛኛው ጊዜ ስለ ሀገር ጉዳይ ከመወያየት ተቆጥበን አናውቅም:: አልፎ አልፎም መከራከራችን አይቀርም:: በሃሳብ ልንለያይም እንችላለን:: በሃሳብ መለያየት ክፋት የለውም። በሃሳብ መለያየታችን ለዲሞክራሲ ግንባታ የበኩላችንን ከማድረግ ሊያግደን አይገባም:: አብረን ከመስራትም ሊያግደን አይገባም::

ዛሬ ነገ ሳንል  ተግባራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ በሀገራችን ኢትዮጵያ የተጀመረውን የለውጥ ጉዞ  ማገዝ ኢትዮጵያዊ ኃላፊነታችንና ግዴታችን ነው:: ተግባር ከብዙ ቃል በላይ ይናገራል ይባላልና እራሳችንን በተግባር የምንፈትሽበት ጊዜ ነው:: ሀገራችን ከአምባገነናዊ ሥርዓት ተላቃ በሽግግር ላይ  ያለች እንደመሆኗ መጠን ከምንም ጊዜ በላይ የልጆቿ እገዛ  ያስፈልጋታል።

ዲያስፖራው  ለውጡን በብዙ መልኩ ማገዝ ይቸላል፣ ዋናው ቁርጠኝነት ነው። 

በሀገራችን የተከሰተው ለውጥ ስር ነቀልና ዘላቂ እንዲሆን ከምንም በላይ የተቋማት ግንባታ ያስፈልጋል:: ሲቪክ ማህበራት፤ ነፃ የሚዲያ ተቋማት፤ ከፖለቲካ ፓርቲ ተፅእኖ የተላቀቀ ሲቪል ሰርቪስ እና ሌሎችም ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት አስፈላጊ የሆኑ ግብዓቶች በሙሉ እንዲሟሉ ዲያስፖራው በብዙ መልኩ እገዛ ማድረግ ይችላል። ይህ ተግባራዊ እንዲሆን ሁሉም በሆደ ሰፊነትና ይቅር ባይነት መንፈስ ሊነሳሳና ነገ የተሻለ ቀን እንዲሆን ሊሰራ ይገባል። ትናንት አብረን ስላልሰራን ነገም አብረን መስራት አንችልም የሚል አመለካከት ጊዜው ያለፈበትና ያረጀ ነው። በፖለቲካው ዓለም ዘላለማዊ ወዳጅ ወይም ዘላለማዊ ጠላት የለም ይባላል። ሁሉም በህሊናው ልክ ነው የሚለውን ነገር ለማሳካት ነው የሚሰራው። በዚህ ሂደት ውስጥ ደግሞ ለድርድር የማይቀርቡ ነገሮች እንደሚኖሩት ሁሉ የጋራ የሚያደርጉን ብዙ ነገሮች አሉ። ኢትዮጵያ የሁላችን ነች። ኢትዮጵያ የጋራችን ነች። ከአንድ ቤተሰብ የተፈጠሩ ግለሰቦች በእናታቸው አይደራደሩም። ወፈርችም ቀጠነች፤ አጠርችም ረዘመች፤ ደሃም ሆነች ሀብታም፤ እናት ሁሌም እናት ነች። ኢትዮጵያም ኢትዮጵያ ናት።

ኢትዮጵያውያን ዲያስፖራዎችን አንድ የሚያደርገን ከምንም በላይ ኢትዮጵያዊነት ነው። ሀገራችን በበጎ እንጂ በክፉ ስሟ አንዲነሳ አንፈልግም። ወደድንም ጠላን ሀገራችን ሀገራችን ነች።  የሀገራችን በኢኮኖሚ ወደ ኋላ መቅረት ጠንክረን በህብረት ያለመስራታችን ውጤት ነው። ለዚህም የነበሩት ስርዓቶች ተፅዕኖ ያደረጉብን መሆኑ የማይካድ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ያገኘነውን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ሀገራችንን ልናግዛትና የበኩላችንን ልናደርግላት ይገባል፣ ይቻላልም። ላለፉት አያሌ አመታት በዓለም ዙሪያ የተበተኑት ኢትዮጵያውያን በየሀገሮቹ ካሉት ኤምባሲዎች ጋር ያላቸው ግንኙነት እጅግ በጣም አናሳ ነበር። በዚህም ምክንያት በዲያስፖራውና በኤምባሲዎች መካከል ያለው ግንኙነት ጥርጣሬ የበዛበትና ብዙ ወደፊት መሄድ የማይችል ነበረ። ይህ የቆየና ስር የሰደደ አመለካከት ከጊዜው ጋር ሊለወጥ ይገባል። መጥፎ ነገሮችን እንደምናወግዝ ሁሉ በጎ ነገሮችን ደግሞ ማወደስና ማበረታታት ይገባል። ኢትዮጵያዊ አብሮ መብላት እንጂ አብሮ መስራት አይችልም የሚለውን የቆየ አባባል ማክሸፍ ይገባል። በልዩነት ላይ ተስማምቶ አብሮ መስራት እንደሚቻል በተግባር በማሳየት የተለወጥን ሰዎች መሆናችንን ማሳየት አለብን። ጊዜው ሲደርስ ዜጎች ከኤምባሲዎቻቸው ጋር መልካም ግንኙነት ፈጥረው ብዙ ለሃገር የሚበጅ ስራ መስራት ይቻላሉ። ያኔ ሁሉም ይሆናል። እስከዚያው ግን ዲያስፖራው በግሉና በተደራጀ መልኩ ብዙ ነገሮችን ማከናወን ይችላል።  

የሚከተሉትን ማከናወን ለሞራል እርካታ ከማገዙም በላይ ሀገራዊ ግዴታን ለመወጣት ይጠቅማል።

1.       የውይይት መድረኮችን፣ ኮንፈራንሶችን፣ ልዩ ልዩ ዐውደ ጥናቶችን በማዘጋጀት ህዝባችን የተገኙትን ለውጦች እውቀቱን፣ ገንዘቡን፣ ጊዜውን በመስጠት በተግባር ማገዝ እንዲችል ማበረታታት።
2.    ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር ዜጎች የገንዝብ እገዛ እንዲያደርጉና ገንዘባቸውም ለታቀደለት ዓላማ እንዲውል ንቁ ተሳትፎ ማድረግ።
3.       ዜጎቻችን ወደ ሀገራቸው በመሄድ እወቀታቸውንና ጊዜያቸውን ለወገኖቻቸው እንዲያካፍሉ ማበረታታት።
4.       ዜጎቻችን ከሀገር ቤት የሚያገኙትን እውቀትና ልምድ በሚኖሩበት ሀገር ለሚገኙ ወገኖች ማካፈል የሚችሉበትን መድረክ ማመቻቸት።
5.       ዜጎች የውጭ ትምህርት እድል እንዲያገኙ ጥረት ማድረግ፣ አስፈላጊ ሆኖ ሲግኝ በተደራጀ መልኩ ማገዝ።
6.       ኢንቨስትመንት ወደ ሀገር ቤት እንዲገባ ማበረታታት::
7.       ሀገራችን ከቱሪስቶች ጉብኝት የውጭ ምንዛሬ ልታገኝ የምትችለበትን ሁኔታ መፍጠር
እነዚህንና ሌሎች ተግባራትን በተደራጅ መልኩ በማከናወን ሀገራዊ ግዴታን በመወጣት ከህሊና ወቀሳም መዳን ይቻላል። ከምንም በላይ ግን ለዲሞክራሲያዊ ተቋማት ግንባታ ዲያስፖራው ከፍተኛ እገዛ ማድረግ ይችላል ። ይጠበቅበታልም።

ቸር እንሰንብት።


The Global Refugee Forum – time for meaningful participation of Refugees

  As the Global Refugee Forum takes place between 13 - 15 December 2023 in Switzerland, it is vital that we have meaningful participation of...